Tuesday, May 05, 2009

"ኤይድስ በዳያስፖራው ኢትዮጵያዊ መንደር! "

ከዲሲ ሕዝብ 3% ያህሉ በኤይድስ በሽታ የተበከለ ነው። አንዳንዶች ማዕከላዊ ቁጥሩ ከዚህም እጥፍ ይሆናል ይላሉ። የጥቁሩን ሕብረተሰብ ብቻ ነጥለን ብንወሰድ 7% የሚሆነው የበሽታው ሰለባ ሆኗል።

ዛሬ የኤይድስ አክቲቢስት መስየ የቀረብሁት በበቂ ምክንያት ነው። በውጭ ከሰፈረው ኢትዮጵያዊ ወገናችን አብዛኛው መቶኛ ዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ የሚኖር ስለሆነ ሁኔታው በግለሰብም፤ በማህበረሰብም ደረጃ ሊያሳስበን ይገባል። ከዚያም አልፎ ሊያስደነግጠን ይገባል። በጤናው መስክ የተሰማራ ወዳጄ በኢትዮጵያዊው ህብረተሰብ ውስጥ የኤይድስ ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱን ያጫወተኝ አይቼበት ከማላውቀው ትከዜ ጋር ነበር። በሱ ግምት የሀበሻው ሕብረተሰብ ተነጥሎ ቢጠና የተለከፈው ወገን ከ 10% እንደማያንስ አልተጠራጠረም። በተለይ ወጣቱ አካባቢ።

የዋሺንግተን ዲሲው ኤች አይቪ ኤይድስ ሁኔታ የወረርሽኝ ያህል አስደንጋጭ ደረጃ ላይ ስለደረሰ የመንግሥትንና የሕብረተሰቡን ትኩረት እያገኘ ነው። በሀበሻው መንደር ግን ግንዛቤውም ድንጋጤውም ጎልቶ አለመታየቱ እጅግ ያሳስባል!

ከወዳጄ ጋር ጭንቅላቶቻችንን ለጥቂት ጊዜ አጋጨንና የሚከተሉትን ቁምነገሮች ልናካፍላችሁ ተስማማን። በዚህ ዓለም ላይ ባለማወቅ ከምናደርጋቸው ስህተቶች እያወቅን የምንፈጽማቸው በጅጉ እንደሚበዙ የሰው ልጅ ታሪክ የመሰከረው ነውና የምናውቀውንም እንደገና መማማራችን አስፈላጊ ነው። ከተወሰነ ፍጥነት በላይ መንዳት ቅጣት እንደሚያስከትል እያወቅን ቲኬት የተከናነብን ስንቶች ነን? በኤይድስ ላይ የሚደረግ ውይይትንም በዚሁ መልኩ እንየው።

ኤይድስ መሠሪና ፈሪ ጠላት ነው። አዕምሮአችን በመጠጥ ወይንም በፍትዎት የተዘናጋበትን ሰዓትና አሳቻ ቦታ መርጦ ያጠቃል። ስለሆነም መጠጥ መጠጣት ካለብን ልካችንን እንወቅ።
ፍትዎት እንደታንጎ ሁለት ደናሺ ይጠይቃል። እኔ ጥንቁቅ ነኝና ጓደኛየም ትንቁቅ ትሆናለች ማለት አይቻልም። ያልተጋቡ ጓደኞች ኮንዶም መጠቀምን ከጀግንነትና ከስልጡንነት ሊቆጥሩት ይገባል። የኮንዶም ፍትዎት ያለኮንዶም ከሚደረግ ፍትዎት እኩል እንደሚጥም አዕምሮአችን ይቀበለው። ባለትዳሮችም ቢሆኑ አንደኛው ወገን በምንም መነሻ ይሁን ስጋት አደረብኝ ካለ “እንመርመር ቀፈፈኝ” ማለትን መፍራት የለበትም። ሌላው ወገንም እንዴት ተደፈርኩ! ብሎ አካኪ ዘራፍ አይበል። ምርመራው ለሁለቱም ይበጃል፤ መተማመንና ፍቅርን ያጠናክራል።
ሀገር ቤትን እንፍራ። አዎን ያገር ቤት ጉብኝትን መፍራት ነው። ያገራችን ሴቶች ቀድሞውንም ቆንጆ መሆናቸው አንሶ አሁን ደግሞ ይበልጡን እያማሩና እያማለሉ ሄደዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ከፍተኛ የኤይድስ ተሸካሚ ከሚባሉት አገሮች አንዷ መሆኗን ስንገነዘብ፤ ሥራ አጥነት ወጣቱን በፍትዎት ንግድ ውስጥ እንዲሰማራና የቤተሰብ ሀላፊነትን እንዲሸከም ያስገደደበት አገር መሆኑን ስናይ፤ “ረሀብ ባንድ ቀን ይገድላል ኤይድስ ፋታ ይሰጣል” የሚሉት አሰቃቂ ቀልድ የነገሰባት አገር ሞሆኗን ስንረዳ፤ ከልማት ይልቅ የቡና ቤቶች የክለቦችና የማሳጅ ፓርለሮች ኢንዱስትሪ እንደ እንጉዳይ የፈሉባት አገር መህኗን ስናስታውስ፤ ሙያ ይመስል አዲሳባ ባንኮክን ሆናለች እያለ የፍትዎት ቱሪዝምን የሚያሞግስ ትውልድ የበረከተበት አገር መሆኗን ስንረዳ ዳያስፖራውያን ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለብን እንረዳለን። ዶላርንና የውሸት ትዳርን አሰፍስፈው የሚጠብቁ እነርሱ አደገኞች ናቸውና እንቆጠብ።

በዋሽንግተን ዲሲ አካባቢ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ በኤይድስ ወረርሽኝ በከፍተኛ መቶኛ የተመታው አገር ቤት ጋር ባለው ንኪኪ እንደሆነ በድፍረት መናገር ይቻላል። በሌላው ያሜሪካ ክፍልና በሌላው ክፍለ ዓለም ያሚኖረውም ኢትዮጵያዊም ከዚህ መቅሰፍት የተከለለ አለመሆኑን መዘንጋት የለበትም።

ገለልተኛነታችን ሊጎዳን መሰለኝ። ሀበሾች ስንባል ከሌላው ስደተኛ ህብረተሰብ በበለጠ በራሳችን ማህበረሰብ ውስጥ ተከልለን መኖርን እንመርጣለን። ይህ ተፈጥሯዊ መነሻ ቢኖረውም ተቋሞቻችን የሚገባንን እንክብካቤና ትመህርት ከሚሰጡበት የዕእድገት ደረጃ ላይ ካልደረሱ ተጎጅዎች እንሆናለን። አሜሪካኖቹ ኤይድስን በሚያክል አደገኛ ጠላት ላይ በሚያካሂዱት ዘመቻ ላንሳተፍ ነው። በዚህ በሽታ የተጠመዱ ወገኖቻችን ተደብቀው እንዲኖሩና ራሳቸውንም ሌሎችንም እንዲጎዱ ሰበብ እየሆንን ነው። ሀበሻው ጋር አድረን ሀበሻው ጋር ውለን ሀበሻው ጋር እስካመሸን ድረስ እንዲህ ያለ አደጋ ይመጣል፡፤

እናስ ታዲያ ምን ይሁን? እናማስ ሀላፊነት እንውሰድ። በየግላችን መውሰድ የሚገባንን ርምጃ በሃላፊነት ስሜት እንወጣ። ልጆቻችንንም ሰብሰብ አድርገን ያለ መሽኮርመም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት ነው። በሞት ፊት መሽኮርመምን ምን አመጣው?

የሀይማኖት የፖለቲካና የማህበራዊ ተቋሞችም ችግሩን እያዩ እንዳላዩ አይሁኑና ይህን መሠሪ ጠላት በመዋጋት ረገድ አመራር ያሳዩን። ሦስቱም ቢሆኑ ጤነኛ ሕብረተሰብ በሌለበት ሊጠነክሩና ሊከበሩ አይቻላቸውም። በንዲህ አይነት ቅዱስ ዘመቻ ውስጥ የነቃ ተሳትፎ ያሚያደርግ ተቋም ከበሬታም ያገኛል የአባላትና የደጋፊ መሠረቱንም ያሰፋል። ኤይድስ በርዕዮተ ዓለምና በሀይማኖት ቀኖና ላይ የሚያሾፍና የሚረታ ሴሰኛ ባላንጣ ነው።


ቁጥር ቀልባችሁን ያስገኝልን እንደሁ ትንሺ በቁጥር እናስደንግጣችሁ። ዊኪፒዲያ የተባለው ድርጅት ለአቅመ አዳም የደረስውን በኤይድስ የተለከፈ ሕዝብ እንዲህ ያስቀምጠዋል። ታንዛኒያ 8.8% ኬንያ 6.7% ኮንጎ 4.9% ኢትዮጵያ 4.4% ። የሲ.አይ.ኤው ርፖርት ደግሞ የኢትዮጵያውን ወደ 10-18% ይተምንና በ 2010ዓ/ም ደግሞ ከ19-27% እንደሚደርስ ያሳስባል።

እንግዲህ የዲሲው ኤይድስ መቶኛ ከሦስተኛው ዓለም መቶኛ መብለጡ ካላስደነገጠን ምን ሊያስደነግጠን እንደሚችል አናውቅም። ዲሲን ከሦስተኛው ዓለም ጋር እንመድበው ይሆን?

Kuchiye@gmail.com

No comments: